ተስፋለም ወልደየስ፦ "ሚዛን" በሳተበት አገር "ሚዛን" ባለ ብዕሩን የተቀማ ጋዜጠኛ (ከዘሪሁን ተስፋዬ)


ሌሊቱ ሊጋመስ ግማሽ ያህል ሰዓት ቀርቶታል። ወትሮም ዓርብ ምሽት ውክቢያ የማያጣው የአዲስ ነገር ቢሮ በግርግር ተሞልቷል። ጋዜጠኛ ወዲህ ወዲያ ይራወጣል። ቀሪው ኮምፒውተር ላይ አፍጥጦ ዘወትር ለሕትመት ዘግይቶ ለሚገባው ጋዜጣ ጽሑፉን ይተይባል። ጋዜጠኛ ተስፋለምም አንዲት ጥጉን ይዞ ይጫጭራል። ዜናዎች ኤዲት ያደርጋል። እኔም ለመጀመሪያ ጊዜ ይዤ የመጣሁትን ዜና ኤዲት እንዲያደረግ ሰጥቼው፤ ወደጀመርኩት የኢኮኖሚ ጽሑፍ ተመለስኩ። ነገር ግን አፍታም ሳይቆይ በንዴት እየቀዘፈ "አሁን በዚህ ሌሊት ይህ ዜና ተብሎ ይሠራል... " ተስፋለም ይህን ይህል ግልጽ ነው። ለሞያው የሚቆረቆር። አንዳች ስህተት መስሎ የሚሰማውን ፊት ለፊት ከመናገር የማይቆጠብ።
ያን ሌሊት በብዙ ጭቅጭቅና ንትርክ ዜናው ተሰርቶ ወጣ። አጋጣሚው ግን ልዩነታችን በጋዜጠኝነት ፍልስፍና ላይ እንደሆነ ቁልጭ አድርጎ ያሳየ ነበር። እሱ "ሚዛናዊ" ብሎ የሚሟገትለት ጋዜጠኝነት በኢትዮጵያ የፖለቲካ ሥራዓት አንዳች የማያራምድ ይልቁንም ጋዜጠኝነትን አሽመድምዶ ልሳን የሚሸብብ መኾኑ ሊያግባባን አልቻለም። እኔ "balanced journalism is a zero-sum game in Ethiopia" ብዬ እሞግተዋለሁ፤ እሱ በየትኛውም የመንግሥት ሥራዓት ቢሆን የጋዜጠኝነት ሕግጋት የማይጣሱ ደንቦች ናቸው ይላል። ይህንንም በሥራው ያሳያል።
ጋዜጠኝነትን ሕይወቱ ያደረገው ተስፋለም፤ በምንም መልኩ ቢሆን ሞያው በትምህርት ቤት ያገኛቸውን የጋዜጠኝነት መርሖዎች እንዲቃረን አይፈልግም። ዜናዎች ሲያዘጋጅ "ሚዛናዊነት" የሚለው መርሕ አለመጣሱን ሲያረጋግጥ ብቻ ነው ወሬው የሕትመት ብርሃን የሚያየው። ይህ ግን በአንዳንድ ባልደረቦቻችን ላይ ጥርጣሬ አልጫረም ማለት አይቻልም። እሱ "ሚዛናዊ" ብሎ የሚጠራው ጋዜጠኝነት፣ ለዘብ የሚል በተለይም አንዳንድ ጠንካራ የሚባሉ ዜናዎችን (በአዲስ ነገር በወቅቱ ዕይታ) አግላይ ነው የሚል ክርክር ይስነሳ ነበር። የዜናዎቹ 'ሚዛን' ለመጠበቅ ሲባል ለዘብተኛ መኾናቸው "ተስፍሽ ለመንግሥት ተቆርቋሪነት ያሳያል" የሚል አንድምታ ያለው ጥርጣሬ ማሳደሩ አልቀረም።
ይሁንና በሚያዘጋጃቸው ዜናዎች ተዓማኒነት፣ ጥራት እና ቋንቋ አጠቃቃም ሁሉም የሚያደንቀው ነበር። በተለይ ማህበራዊ ገጾች ላይ የሚወጡ ጽሁፎችን እሱ ሳያይቸው እንዲወጡ የሚፈልግ ጋዜጠኛ አልነበረም። የመተረክ ችሎታው፤ የቋንቋ አጠቃቀሙ እና ዝርዝር ጉዳዮችን የማካተት ብቃቱ ልዩ ነው። ተግባቢነቱና ሁለ ገብነቱም የሞያ መርሕ ልዩነት ቢኖርም በሁሉም ዘንድ በፍቅር እንዲፈለግ አድርጎታል። የማይደክም ነው። የእንቅልፍ ሰዓቱ እጅግ በጣም አነስተኛ መሆኑ እንደ ሰው ቆሞ መሄዱ ሁሌም የሚገርመኝ ነው።
ዙረት ይወዳል። በአንድ ሥፍራ መቀመጥ የጋዜጠኛ ተግባር አይደለም ባይ ነው። በመጓዝ ጋዜጠኛ በእውቀት ይበለጽጋል የሚል ዕምነት አለው። ወደ ተለያዩ አገሮች በሚጓዝበት ወቅት ብዙ ጋዜጠኞች የማይሳካላቸውን የጉዞ ማስታዎሻዎችን ማዘጋጀት ላይ የላቀ ብልጫ እንዳለው አሳይቷል። በአንድ ጉዞ ብቻ ለወራት የሚበቃ ታሪክ ይዞ ይመለሳል።
የተስፋለም "ሚዛናዊነት" መርሕ ቢያንስ ቢያንስ ሚዛን የሳቱ አስተዳዳሪዎቻችንን ብትር እንዳይቀምስ ከለላ ይሆነዋል የሚል ዕምነት ነበረኝ። ግምቴ ግን አልሰራም። ሁሌም ጠላት ከጉያው ሥር ካልፈለቀቀ ያስተዳደረ የማይመስለው መንግሥት ተስፋለምን በጠላትነት ፈረጀው። ማዕከላዊ እስር ቤትን ለዜና ሥራ እና እሥረኛ ወዳጆቹን ለመጠየቅ ብቻ የሚሄድበት ጋዜጠኛ፤ አሁን ማደሪያው ኖኗል። እጅግ ልብ የሚሰብር ኢ-ፍትሓዊነት ነው። በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ታሪክ ውስጥ ይሄን ያህል ለሞያ ታማኝ መሆን የሚያስከፍለው ዋጋ እስር እና እንግልት መሆኑ አሳዛኝ ነው።
የተስፋለም እስር ኢ-ፍትሓዊነት ብቻ አይደለም ጸጸት የሚፈጥረው። ብዙዎቻችን የሥራ ባልደረቦቹ ይህንን እውነታውን ሳንረዳ መቅረታችን ነው። ስለዚህች አገር ተስፋ ነበረው። አዎንታዊ ጉዳዮችን ይበልጥ መፃፍ መንግሥትን ከአውሬነት ወደ ሰለጠነ ሰውነት ይገራዋል የሚል ዕምነት ነበረው። እምነቱ ግን ተስፍሽን ዕራሱን አስከፈለው። ሚዛን የሳተኝ አገር ሕሊና ቢሶች አስተዳዳሪዎች ተሸክማ ተስፋለምን ለአውሊያዋ መገበሪያ አደረገችው። ብዕሩን ነጥቃ ከሚወደው ሞያ ለጊዜውም ቢሆን ለየችው።
ተስፋለምን ከሞያ ባሻገርም እንደ ቅርብ ወንድም እናፍቀዋለሁ። ከነልዩነታችን የጥበብ ፍቅር ያስማማናል። ሁለታችንም ዙረት መውደዳችን በተለያየ አጋጣሚ የተለያዩ ሥራዎች እንድንሰራ አድርጎናል። ከሁሉ ግን ዑጋንዳ ለሥራ ለዓመት በቆየበት ጊዜ የመጀመሪያውን በምስራቅ አፍሪካ የሚሰራጭና በአማርኛ የሚታተም "ሐበሻዊ ቃና" የሚል በስደተኞች ላይ የሚያተኩር ጋዜጣ መጀመሩ ይበልጥ እንደወደው አድርጎኛል- ለሞያውም ጥልቅ ፍቅር እንዳለው መስክሮልኛልና።
ተስፍሽን ባልደረቦቹ በወጉ አልተረዳነውም። ፍቅርና አክብሮታችን ግን ሁሌም ነበር። አሁንም ይበልጥ እንድናከብረው ለሚዛናዊነትም የከፈለውን መስዋዕትነት እንድናስበው ሆኖል። ተስፍሽ ሁሌም የምታከብራት ሚዛናዊነት ከግፈኞች አሳሪዎችህ ነጻ በምትወጣ አገራችን ነፍስ ዘርታ እንደምትላወስ አትጠራጠር። (ዘሪሁን ተስፋዬ)

No comments:

Post a Comment